የአዋሽ ባንክ የባለአክሲዮኖች 26ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ህዳር 18 ቀን 2014 ዓ.ም በአዲስ አበባ ሒልተን ሆቴል ተካሂዷል፡፡ በስብሰባውም ላይ የአዋሽ ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ አምባሳደር ዶ/ር ዲባባ አብደታ በተጠናቀቀው የ2020/21 የሂሣብ ዓመት አዋሽ ባንክ በሁሉም የሥራ ዘርፎች አመርቂ ውጤቶችን ማስመዝገቡንና ከግል ባንኮች የመሪነት ሥፍራውን ለተከታታይ ዓመታት ይዞ መቀጠሉን አስረድተዋል፡፡ በባንኩም የ10 ዓመት ፍኖተ ካርታ መሠረት እ.ኤ.አ. 2025 መጨረሻ ላይ ከአሥር ምርጥ የምሥራቅ አፍሪካ ባንኮች መካከል አንዱ ለመሆን ያስቀመጠውን ግብ በተሳካ ሁኔታ እያሳካ መሆኑን የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢው ገልጸዋል፡፡
ባንኩ ይህንን አመርቂ ውጤት ማስመዝገብ የቻለው በዓለም አቀፍ እና በአገር አቀፍ ደረጃ የተደቀኑበትን ፈተናዎች ሁሉ ተቋቁሞ ስለሆነ ለዚህ ውጤት ያበቁትን አካላት ማለትም የዳይሬክተሮች ቦርድ አባላትን፣ የሥራ አመራር አባላትንና ሠራተኞችን፣ ባለአክሲዮኖችን፣ ደንበኞችን፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑትን አካላት ሁሉ አመስግነዋል፡፡